Friday, April 26, 2013

ሆሣዕና


ሆሣዕና እና ምሳሌነቱ
ማቴ 21፡1-10


ሆሣዕና ማለት መድሃኒት ማለት ነው፡፡
ደብረ ዘይት ወይራ የበዛበት ተራራ ነው፡፡
ቤተ ሳጌ የድሆች መንደር ናት፡- ጌታ የድሆች መንደር ወደደ፡፡እኛ ድሆቹን ባለ ፀጋ ሊያደርገን ስለኛ ብሎ ራሱን ድሃ ያደረገ አምላክ ነውና፡፡
ቤተ ሳጌ ለእየሩሳሌም በጣም ቅርብ ናት፡፡እኛም ለቤተ ክርስትያን ቅርብ መሆን አለብን፡፡
እየሩ ሳሌም ቤተ ክርስትያን ናት እንቅረባት 
እየሩ ሳሌም እመቤታችን ናት እንቅረባት
ጌታ ቤተሳጌ በደረሰ ጊዜ የተመሳቀለ መንገድ ቁሞ ሁለቱን ደቀ መዛሙርቱ ላከ
*ሁሩ ሃገረ ቅድመክሙ* ወደ ፊታችሁ ላለው ሃገር ሂዱ ወደ መንደሪቱ ግቡ አላቸው፡፡ 

በተመሳቀለ ቦታ መቆሙ፡- ወደ ፊት በመስቀል ላይ እሰቀላለሁ ሲል ነው፡፡
ሁለቱ ደቀ መዛሙርቱ ሲልካቸው በፊታችሁ ላለው ሃገር ሂዱ ያን ጊዜ አህያ ከውርንጭላዋ ጋር ታስራ ታገኛላችሁ ፈታችሁ አምጡልኝ አላቸው፡፡ 

ጌታችን ብዙ ያልታሰሩ አህዮች እያሉ ለምን የታሰሩትን መረጠ?

አህዮቹ የታሰሩት ሌባ ሰርቆ ነው ያሰራቸው፡፡ ወንበዴ ሰርቆ ነው ያሰራቸው 
አህዮቹ ለጌታ ውለታ ሰርተዋል፡፡ ጌታ ሲወለድ አሙቀውታልና፡፡ ለጌታ ውለታ ልንመልስ ያልቻልነው እኛ ሰዎች ብቻ ነን፡፡

የታሰሩት እዲፈቱ የመረጠበት ሚስጥር

እኔ ከሃጥአታችሁ ልፈታችሁ የመጣሁ ነኝ ሲል ነው፡፡
ወንበዴው አህዮቹን ሰርቆ በመንደር እንዳሰራቸው ዲያብሎስም ለሰው ልጅ በሃጥአት ሰንሰለት ከሲኦል መንደር አስራቸው ነበርና፡፡
ሃዋርያቱ ሲልካቸው ምን ታደርጋላችሁ የሚላችሁ ሰው ቢኖር ጌታቸው ይሻቸዋል በልዋቸው አላቸው፡፡ የፈጠራቸው እሱ ነውና፡፡ 

ከአህያዋ ጀርባ ሃዋርያት ልብሳቸው አነጠፉለት ለምን?

ለምንስ ኮርቻ አላደረጉለትም? ለምንስ ልብሳቸው መረጡ? 
ለስላሳ ህግ የሰራህልን አንተ አባት ነህ ሲሉ ነው
ለስላሳ ህግ የተባለው ወንጌል ነው
ወንጌል ፍቅር ናት የሚረግማችሁ መርቁ ትላለችና፡፡
ልብስ የሰውነት ነውር ይሸፍናል፡፡ ነውረ ሃጥአታችን የምትሸፍንልን አምላክ ነህ ሲሉ ነው፡፡ እሱ ልብሳችን ነውና፡፡ ነውራችን የሚሸፍንልን እሱ ነውና፡፡
ችግሩ ግን ነውረ ሃጥአታችን የሚሸፍንልን ልብስ እርሱ መሆኑን አለማወቃችን ነው፡፡
አብሮን እንዳለ አለማስተዋላችን ነው፡፡ 
ስለዚ እደ ሃዋርያት ነውረ ሃጥአታችንን አስቀድመህም የሸፈንክልን ዛሬም የምትሸፍንልን ወደፊትም የምትሸፍንልን አምላክ አንተ ነህ ልንለው ይገባል፡፡

ጌታችን በሁለቱ አህያዎች በጥበብ ተቀመጠ፡- በሰው የማይቻል በእግዚአብሔር ዘንድ ግን የሚቻል መሆኑ ጥበበኛ አባት ሁሉን የሚችል አባት መሆኑ የሚገልጽ ነው፡፡ አንድም ወንጌልን ኦሪትና ሃዲስን ሁለቱ አስታርቆ አስማምቶ አንዱን አንዱን እየመገበ የሚሄድ መሆኑ የሚያመለክት ነው፡፡

ጌታ ለምን በፈረስ ላይ አልተቀመጠም?

ትንቢትና ምሳሌውን ለመፈጸም ነው፡፡ ት.ዘካ9፡9 ፃዲቅ የባህሪ አምላክ የዋህ ሃዳጊ በቀል ንጉስሽ በአህያ በወርንጭላዋ ተቀምጦ ይመጣል ብላችሁ ለጽዮን ልጅ ንገርዋት ብለዋልና፡፡

ፈረስ
• ተንኮለኛ ናት ለጠላትዋም አውድቃ ረግጣ ትገድላለች
• ረጋ ብላ መሄድ አትችልም ትቸኩላለች
• ልትወጣባት ስትልም ታስቸግራለች አትመችም ተነጣጥረህ ነው የምትወጣባት 
• ጌታ የወደደውና በትንቢቱም እደተገለጸው አህያን መረጠ፡፡

በአህያ መቀመጡ
• ትህትናን ለማስተማር
• የሰላም ዘመን ነው ሲል 
• ለፈለጉኝ ሁሉ የቅርብ አምላክ ነኝ ሲል በንጽህና በየዋህነት ለሚኖሩ መእመናን አድሬባቸው እኖራለሁ ሲል፡፡
• አህያዎች ትሁታን ናቸው ረጋ ብለው ነው የሚሄዱት፤በቀላሉ ትወጣበታለህ፤በቀላሉ ትይዘዋለህ፤እንደፈለክም ታዝዋለህ፤እኛ በትእቢት ተይዘን ነው እንጂ በየዋህነት ብንመላለስ እሱ ያድርብን ነበር፡፡ እኛ የእግዚአብሔር ማደርያ ነንና፡፡

ትልቅዋ አህያ የኦሪት ምሳሌ ነው
1. ትልቅዋ አህያ ሸክም የለመደች ናት ህገ ኦሪትም የተለመደች ህግ ናትና፡፡
2. የእስራኤል ምሳሌ ነው፡-ትልቅዋ አህያ ሸክም እንደለመደች ሁሉ እስራኤልም ህግ ለመፈጸም በህግ ለመራመድ የለመዱ ናቸው፡፡
3. የአዳም ምሳሌ ነው፡- አዳም ሸክም የበዛበት ነበርና 

ውርጭላዋ
1. በህገ ወንጌል ትመሰላለች፡-ምክንያቱም ወንጌል ኢየሱስ ክርስቶስ የመሰረታት የሰራት አዲስዋ ህግ ናትና፡፡
2. በአህዛብ ትመሰላለች፡-ትንሽዋ አህያ ሸክም የለመደች አይደለችም እንዲሁም አህዛብም ህግህን የመቀበል የለመደ አይደሉም፡፡ ለህግህ አዲስ ናቸውና፡፡
3. የእመቤታችን ምሳሌ ናት፡- የዓለም ሸክም አቅልላለችና በእመቤታችን ትመሰለላለች፡፡ እመቤታችን ድህነተ ምክንያታችን ጌታን የተሸከመች ንጽህት እንከን የሌላት እናት ናትና፡፡


ህዝቡም ልብሳቸው እያወለቁ በጎዳና አነጡፉለት ለምን?

እንኮን አንተ የተቀመጥክባት አህያም ክብር ይገባታል ብለው ነው፡፡ 
እስራኤላውያን ጌታ የተቀመጠባት አህያ አከበሩ፡፡ ይህ ትውልድ ግን ጌታ የተቀመጠባት እመቤታችን ማክበር ተሳናቸው፡፡
ልብሳቸው ማንጠፋቸው፡- ለክብሩ መግለጫ ነው፡፡

ሌሎችም ቅጠል አነጠፉለት፡ ሶስት አይነት ቅጠል አነጠፉለት
ዝንባባ፤የቴመር ዛፍ፤የወይራ ዛፍ አነጠፉለት፡፡


ዝንባባ
1. ዝንባባ፡- ይስሃቅ በተወለደ ጊዜ ደስ ብሎት አብርሃምን ዝንባባ ይዞ እግዚአብሔር አመስግነዋል፡፡
2. ዝንባባ ደርቆ እንደገና ሂወት ይዘራል፡- የደረቀ ሂወታችን የምታለመልም አምላክ ነህ ሲሉ ነው፡፡
3. ዝንባባ የሰላም ምልክት ነው፡- የሰላም አምላክ ነህ ሲሉ ነው
4. ዝንባባ የደስታ መግለጫ ነው፡- አንተ ደስ የምታሰኝ ሃዘናችንም የምታርቅልን አምላክ ነህ ሲሉ ነው፡፡
5. ዝንባባ እሾሃማ ነው፡- አንተ ህያው አሸናፊ አምላክ ነህ ሲሉ ነው፡፡
6. ዝንባባ እሳት አይበላውም ለብልቦ ይተወዋል እንጂ፡፡ ጌታም አንተ ባህሪህን የማይመረመር ነው ሲሉ ነው፡፡

የቴምር ዛፍ፡-
1. የቴምር ፍሬ መራራ ጣፋጭም ነው፡- በሃጥአት የመረረውን ሂወታችን የምታጣፍጥልን አምላክ ነህ ሲሉ ነው፡፡
2. የቴምር ዛፍ ከፍ ያለ ነው፡-አንተ አምላካችን ልዑለ ባህሪ ነህ፡፡ ከፍ ከፍ ያልክ አምላክ ነህ ሲሉ ነው፡፡
3. የቴምር ፍሬ በውስጡ ያለውን አንድ ነው፡-አንድ አካል አንድ ባህሪ ነህ ሲሉ ነው፡፡
4. የቴምር ፍሬው በእሾህ የተከበበ ነው፡- ይህም የአንተ ባህሪ የማይመረመር በእሳት የተከበበ ነው ሲሉ ነው፡፡ 


የወይራ ቅርንጫፍ ዛፍ
1. የወይራ ቅጠል ከእንጨት ሁሉ ጽኑ ነው፡፡ አንተም ጽኑ ሃያል አምላክ ነህ ሲሉ ነው፡፡
2. ወይራ ለመብራት ያገለግላል ዜት ያወጣል፡- ከወይራ የሚገኝ ዘይት ጨለማን አሸንፎ ብርሃን እንደሚሰጥ ሁሉ አንተም ጨለማ ሂወታችን የምታስወግድልን አምላክ ነህ ሲሉ ነው፡፡
3. በኦሪት ጊዜ ከወይራ የተገኘ ዘይት ለመስዋእትነት ይቀርብ ነበር፡፡ አንተም እንደ ዘይቱ ለመስዋእት የምትቀርብ አምላክ ነህ ሲሉ ነው፡፡ በመስቀል ላይ መስዋእት ሁነዋልና፡፡


ሆሣዕና በእጃችን እደ ቀለበት ማሰራችን የምን ምሳሌ ነው?

1. ጌታ ለአዳም የሰጠው ቃል ኪዳን ለማስታወስ፡-ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድነሃለሁ ያለውን የተስፋ ቃል ለማስታወስ፡፡
2. ጌታ ለእመቤታችን የገባላትን ቃል ኪዳን ተምሳሌት ነው
3. ጌታ ለእስራኤላውያን የሰጣቸው ቃል ኪዳን ተምሳሌት ነው
4. ጌታ ለአዳም ከሰይጣን ግዛት ነጻ እንዳወጣው ሁሉ እኛም ከሰይጣን ግዛት ከመከራ ስጋ ከመከራ ነፍስ ከክፋት ከሃጥአት አውጣን ማረን ለንስሃ ሞት አብቃን ከቤትህ አትለየን እንደ ቸርነትህ ይቅር በላን ስንል ከጌታ ደግመን ላናጠፋ ቃል የምንገባበት ነው፡፡
ስለዚ እንደ ታሰሩ አህዮች መፈታት አለብን፡፡ ሁላችን ታስረናልና ቤተ ክርስትያን በመሄድ እንድንፈታ እናድርግ፡፡ የታሰሩት ሁሉ በካህናት አባቶቻችን አማካኝነት እዲፈቱ ልናድርግ ይገባናል፡፡ ለምን ቢባል አምላካችን ይፈልገናል አባታችን አማላካን ንጉሳችን ይፈልገናል፡፡ ጌታ ጸጋውን አብዝቶ ለዘላለሙ ከቤቱ አይለየን የነጻነት አባት ካለን ሱስና ልማድ ሁሉ ነጻ አድርጎ ለሱ እንድንገዛ እርሱ ይርዳን አሜን መልካም በዓል፡፡

No comments:

Post a Comment